የኢትዮጵያ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ጉባዔ ወቅቱን ጠብቆ እንዳይካሄድ ያደረጉ እንቅፋቶችን አጣርቶ ውሳኔ በመስጠት፣ ጥር 30 ቀን 2009 ዓ.ም. ጠቅላላ ጉባዔውን እንዲጠራ የሚያችለው ስምምነት ተደርሶ ነበር፡፡
ምክር ቤቱን እየመራ ያለው ቦርድ እንዳጋጠመው ባስታወቀው ችግር ላይ 18ቱን አባል ምክር ቤቶች ጠርቶ በማማከር አጣሪ ግብረ ኃይል ተመሥርቶ ሲያካሂድ የቆውን የማጣራት ሥራ አጠናቆ ሪፖርት አቅርቧል፡፡ ግብረ ኃይሉ ባካሄደው ማጣራት መሠረት ጠቅላላ ጉባዔውን ለማካሄድ እንቅፋት የነበሩ ችግሮች ታውቀው ውሳኔ መተላለፉ አይዘነጋም፡፡ በዚሁ የማጣራት ሥራ የተገኙ የሕግ ጥሰቶች ላይ ግብረ ኃይሉ ዕርምጃ እንዲወስድ ኃላፊነቱን ለምክር ቤቱ ጽሕፈት ቤትና ለቦርዱ ቢሰጥም፣ ውሳኔ ሳይሰጡ ቀርተዋል፡፡ ይህ በሆነበት ወቅት ንግድ ሚኒስቴር ነገሩን ራሱ እንደሚጣራ በማስታወቅ ሊካሄድ የታቀደውን ጉባዔ ታግዶ እንዲቆይ ማድረጉን መዘገባችን ይታወሳል፡፡
የሚኒስቴሩ ውሳኔ በሌሎች ዕይታ
ንግድ ሚኒስቴር ጥር 30 ቀን 2009 ዓ.ም. ሊካሄድ የነበረውን ጠቅላላ ጉባዔ እንዳይካሄድ የሚያግድ ድምዳሜ ላይ መድረሱን ካሳወቀ በኋላ፣ ሪፖርተር ያነጋገራቸውና ለንግድ ምክር ቤቱ ቅርበት ያላቸው ወገኖች የሚኒስቴሩ ውሳኔ ቢዘገይም ተገቢ እንደሆነ ግን ያምናሉ፡፡
መንግሥት የንግድ ምክር ቤቱን ጉዳይ ለማጣራት መወሰኑ ተገቢ ነው ከሚሉት ወገን የሆኑት የደቡብ ክልል ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ፕሬዚዳንት አቶ አሸናፊ ከበደ ናቸው፡፡ በአባል ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤቶች ውስጥ የታዩ የሕግ ጥሰቶችን የተመለከቱ አቤቱታዎች ቀርበውለት አገር አቀፉ ምክር ቤት መልስ ሳይሰጥ መቆየቱ ለችግሩ መባባስ ምክንያት እንደሆነ ለሪፖርተር የገለጹ ሌላ አስተያየት ሰጪም፣ ንግድ ሚኒስቴር ውሳኔ ለማስተላለፍ ዘገምተኛ ሆኖ መቆየቱን ጠቅሰዋል፡፡
መንግሥት በግድ ምክር ቤቶች ውስጥ እጁን ላለማስገባት በመጠንቀቅ ችግሮቹን አባላቱ ራሳቸው እንዲፈቱ ዕድል መስጠቱ እንደሚደገፍ የሚገለጹት አስተያየት ሰጪዎች፣ ይሁንና በአንዳንድ ምክር ቤቶች አመራሮች አማካይነት ይፈጸሙ የነበሩ የሕግ ጥሰቶች ላይ እልባት ለመስጠት አፋጣኝ ውሳኔ አለመሰጠቱ ግን ደካማ የንግድ ምክር ቤቶች እንዲበራከቱ፣ ጥቂት ግለሰቦች ብቻ እየተፈራረቁ ወደ አመራር መንበሩ ለመምጣት የቻሉበትን በር ከፍቷል በማለት የተቹም ነበሩ፡፡
የንግድ ምክር ቤቶች አስፈላጊነትና ጠቀሜታ ለመንግሥትም ጭምር መሆኑ እየታወቀ፣ አሠራራቸውን ችላ ማለቱ የፉክቻ አምባ እንዲሆኑ ማድረጉን በመገንዘብና ችላ ብሎ መቆየቱ ስህተት እንደነበር በማመን ከዚህ በኋላ መንገዳቸውን የማስተካከል ኃላፊነት አለበት በማለት የገለጹ አሉ፡፡
ንግድ ሚኒስቴር ሰሞኑን ባስተላለፈው ውሳኔ የማጣራት ሥራውን ሠርቶ ጠቅላላ ጉባዔው እንዲካሄድ፣ አዳዲስ የአመራር አባላት እንዲመረጡ በማድረግ ብቻ መገታት እንደሌለበትም እየተነገረ ነው፡፡ አስተያየት ሰጪዎቹ እንደሚሉት፣ ለንግድ ምክር ቤቶች መዳከም፣ ጠንካራ መሪዎች ለማግኘት አለመቻል እንዲሁም እንደሌሎች አገሮች ንግድ ምክር ቤቶች ድምፃቸው የሚሰማ ጠንካራ ተቋማት እንዳይሆኑ ካደረጉ ምክንያቶች መካከል የንግድ ምክር ቤቶች ማቋቋሚያ አዋጅና አዋጁን ለማስፈጸም የጠሩ፣ ግልጽ ደንብና መመርያዎች አለመኖራቸው ይጠቀሳል፡፡ ንግድ ሚኒስቴር እንዲህ ያሉ ጉዳዮች እንዲጣሩ ማድረግ ይጠበቅበታል ተብሏል፡፡ ከበርካቶች አስተያየት መረዳት እንደተቻለው፣ የንግድ ምክር ቤቶች ማቋቋሚያ አዋጅና የዘርፍና የንግድ ምክር ቤቶች ሚና በግልጽ እንዲቀመጥ አዋጁ መሻሻል እንዳለበት ነው፡፡
ይህ የማይደረግ ከሆነ ጣልቃ መግባቱ ፋይዳ የሌለውና ችግሮቹ ውሎ አድሮ ዳግመኛ ስለሚፈጠሩ የማጣራቱ ሥራ ጠቅላላ ጉባዔና ምርጫ በማካሄድ ብቻ መወሰን የለበትም የሚሉ የምክር ቤቱ አባላት ጥቂት አይደሉም፡፡
የአቶ አሸናፊ አመለካከትም ከተቀሩት አስተያየት ሰጪዎች ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡ ዘላቂ መፍትሔ ለማስፈን ንግድ ሚኒስቴር ደጋግመው ምክር ቤቶችን እየጎበኙ ለሚገኙ ችግሮች ዘላቂ መፍትሔ ይሰጣል የሚል እምነት አላቸው፡፡
ምክር ቤቱን የሚመራው ማን ነው?
የንግድ ምክር ቤቶቹ ችግር ብቁ መሪዎች ያለማግኘት እንደሆነ ይነገራል፡፡ የንግድ ኅብረተሰቡን ለማገልገል ቅንነቱና ፍላጎቱ ያላቸው፣ የበቁ አመራሮች በየንግድ ኩባንያዎች ቢኖሩም ወደ ንግድ ምክር ቤት የሚመጡት ጥቂቶቹ ናቸው፡፡ የሚመጡትም ብቃታቸው ላይ ጥያቄ እየተነሳባቸው ነው፡፡ የንግድ ምክር ቤቶች አመራሮች የብቃት ጉዳይ ለችግሩ መንስዔ እንደሆነ ሪፖርተር ያነጋገራቸው ሰዎች ያምናሉ፡፡
‹‹በትክክል ነጋዴ ናቸው ብዬ ለመናገር እቸገራለሁ፡፡ እጠራጠራለሁ፤›› ያሉት አስተያየት ሰጪ፣ የራሳቸው ድርጅት እያላቸው ሙሉ ጊዜያቸውን የሚያጠፉት ንግድ ምክር ቤቶቹን ለመምራት እየሆነ መታየቱ ለጥርጣሬያቸው መነሻ እንደሆነ ያስቀምጣሉ፡፡ በተለያዩ የምርጫ ዘመኖች ከአንዱ ወደ ሌላኛው ንግድ ምክር ቤት እየተሸጋገሩ አንዳንዴም በሁለትና ሦስት ንግድ ምክር ቤቶች ውስጥ ራሳቸውን በአመራር ቦታ ላይ እያስቀመጡ የሚታዩ ግለሰቦች፣ በትክክል የንግዱን ኅብረተሰብ እያገለገሉ ስለመሆናቸው አፍን ሞልቶ መናገር አዳጋች እንደሆነ አብራርተዋል፡፡
በመሆኑም ንግድ ምክር ቤቶችን ለመምራት የሚቀርቡ ግለሰቦች ንግድ ፈቃድ ያላቸው ነጋዴዎች ብቻም ሳይሆን በንግድና ኢንቨስትመንት መስኮች አስተዋጽኦ ማድረጋቸው ሊፈተሽ እንሚገባም የሚሞግቱ አልጠፉም፡፡ ከችግሮቹ ትልቁ ችግር ይኸው እንደነበር የሚገልጹት አስተያየት ሰጪዎቹ፣ ንግድ ሚኒስቴር በሕጋዊ መንገድም ሆነ ሕግ ጥሰው ወደ አመራር ለመሆን የሚዳክሩ ወገኖችን ትክክለኛ ነጋዴዎች ስለመሆናቸው፣ ያላቸው የንግድ ድርጅት በአግባቡ እየሠራ የሚገኝ ስለመሆኑ ማጣራት የሚቻልበትን አሠራር እንዲቀርጹ ምክር ቤቶችን እንዲያስገድድ ጠይቀዋል፡፡
በአገር አቀፍ ወይም በክልል ደረጃ የንግዱን ኅብረተሰብ የሚመሩ ወገኖች በግል ቢዝነሳቸው ውጤታማ ሊሆኑ ስለሚገባ፣ የንግድ ሚኒስቴር የቤት ሥራም እንዲህ ያለውን ጉዳይ ማጣራት መሆን አለበት ተብሏል፡፡
ንግድ ምክር ቤቶችን ለመምራት የሚታየው ብርቱ ፍላጎት ብዙዎችን ግራ ያጋባል፡፡ ጥቂት የማይባሉና አሁንም ድረስ በአመራር ደረጃ ላይ ያሉ የንግድና ዘርፍ ማኅበራት አመራሮች በያዙት ቦታ ለዓመታት ለመቆየት እንዲሁም ወደ ኢትዮጵያ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት በፕሬዚዳንትነት፣ በምክትል ፕሬዚዳንትነትና በቦርድ አባልነት ለመመረጥ የሚያደርጉት ሩጫ እርስ በራሳቸው እንዲሻኮቱ ሲያደርግ ቆይቷል፡፡ ከጥቂት ወራት ወዲህ የታየው ትርምስም የጥቂት ግለሰቦች የሥልጣን ፍላጎት ጫፍ መድረስ ውጤት ነው እየተባለ ነው፡፡
በፈቃደኝነት ላይ የተመሠረተ አሠራር የሚከተል በመሆኑ፣ ለንግድ ምክር ቤቶች ኃላፊ ሆኖ መሥራት በቀጥታ የሚያስገኘው ክፍያ ወይም ደመወዝ የለም፡፡ ነገር ግን የኃላፊነት ቦታው በብርቱ ያነታርካል፡፡ ይህ መከሰቱም ነው በሕግ የተቀመጠውን የአንድ ዘመን ጠቅላላ ጉባዔ ለማካሄድ ያላስቻለው፡፡ ችግሮች የተፈጠሩት በአንድ በኩል ጥቅም የለውም እየተባለ በሌላ በኩል ግን ቦታውን ለማግኘት የሚከፈለው መስዕዋትነት ነው፡፡ ተመራጮቹ ቦታውን የግል መጠቀሚያ እያደረጉት ነው የሚል ቅሬታ የሚያሰሙ ወገኖች ጥቂት አይደሉም፡፡ ለዚህ በተለይ የሚጠቀሰው የውጭ ጉዞዎች ጉዳይ ነው፡፡ ለንግድ ጉብኝት ወደ ውጭ የሚጓዙበትን ዕድል እያገኙ በዚያው የሚቀሩ አመራሮች መታየታቸውም ይነገራል፡፡ የውጭ ጉዞዎችን ለማይመለከታቸው ሰዎች በመስጠት ወደ ውጭ እየላኩ ገንዘብ አካብተዋል እየተባሉ ውስጥ ውስጡን ከሚወራባቸው አልፎ በአሁኑ ወቅት ይፋ የወጣ አነጋጋሪ ድርጊት መሆኑም ይገለጻል፡፡
የውጭ ጉዞው የሚመለከተው ባለሙያ ወይም አመራር እንዳይሄድ በማድረግ የቢዝነስ ጉዞዎችን ለሽርሽርና ለመሰል የግል ጉዳይ ማዋልም አመራሮች የሚታሙባቸው ድርጊቶች ሆነዋል፡፡ በቅርቡ የንግድ ምክር ቤቱን ችግሮች እንዲመረምር የተቋቋመው ግብረ ኃይል ሪፖርቱን ሲያቀርብ፣ በንግድ ምክር ቤቶች ውስጥ አጨቃጫቂ ከነበሩና ይጣሩ ከተባሉ ጉዳዮች ውስጥ አንዱ ይኸው የውጭ ጉዞን የተመለከተ መሆኑ የሚታወስ ነው፡፡ እከሌ ይህንን ያህል ጊዜ የጉዞ ዕድል ተሰጥቶታል፣ አቶ እከሌ ደግሞ ገና ኃላፊነት ላይ በወጣ በወራት ጊዜ ሁለቴ አሜሪካ ሄደ የሚሉ ስሞታዎች ሪፖርቱ በቀረበበት ወቅት ተደምጠዋል፡፡
አጣሪ ኮሚቴው የጉዞ ፕሮግራሞች ሥርዓት ሊኖራቸው ይገባል፣ ዕድሉን አግኝቶ የሄደ አመራርም ከጉዞ መልስ ስለሄደበት ጉዳይ ማብራሪያ ያቅርብ የሚል ውሳኔ አሳልፏል፡፡ ለችግሩ ዘላቂ መፍትሔ እንዲሰጥ ንግድ ሚኒስቴር ይህንን አሠራር መፈተሽ አለበት ተብሏል፡፡
‹‹ሳይመረጡ የተመረጡ››
ተደጋግሞ ሲዘገብ እንደከረመው በአገር አቀፍ ንግድ ምክር ቤቱ አባል ምክር ቤቶች ሳይመረጡ ወደ ኢትዮጵያ ንግድ ምክር ቤት መጥተዋል ተብለው ለንግድ ሚኒስቴር አቤቱታ ከቀረበባቸው መካከል አንዱ የአማራ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ነው፡፡
ንግድ ምክር ቤቱን ላለፉት ስምንት ዓመታት በፕሬዚዳንትነት የመሩትና ከጥቂት ወራት በፊት በተደረገ ምርጫ ድጋሚ የተመረጡት አቶ ጌታቸው አየነው፣ ከእሳቸው ጋር አብረው የተመረጡ ሌሎች አመራሮችም ቦታውን የያዙት ከመጡባቸው ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤቶች በሕጋዊ መንገድ ሳይወከሉ ነው የሚል አቤቱታ ከአባል ምክር ቤቶች ቀርቧል፡፡ አቤቱታው ንግድ ሚኒኒቴር ዘንድም ደርሶ ነበር፡፡
በንግድ ምክር ቤቶች ማቋቋሚያ አዋጅ መሠረት በዋናው ንግድ አባልነት የተካተቱ ምክር ቤቶች ምርጫ አካሒደው ወደ ላይኛው ዕርከን መሄድ ይገባቸዋል፡፡ የአማራ ክልል ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ግን አቶ ጌታቸው አባል የሆኑበት የባህር ዳር ንግድ ምክር ቤት ጠቅላላ ጉባዔ ሲያካሂድ ከባህር ዳር መወካለቸው ተነግሮ የተመረጡ ናቸው በማለት የሕግ ጥሰት እንደተፈጸመ አስታውቋል፡፡ አቶ ጌታቸው በወቅቱ በሰጡት ምላሽ እሳቸውና ሌሎች አመራሮች ከታች ምክር ቤት መወከል ሳያስፈልጋቸው በቀጥታ የክልሉ ጠቅላላ ጉባዔ አባል መሆን እንደቻሉ፣ ይህም ከዚህ ቀደም በተደረገ ጠቅላላ ጉባዔ የተወሰነ በመሆኑ የሕግ ጥሰት አለመፈጸማቸውን መግለጻቸው ይታወሳል፡፡
በተመሳሳይ የኢትዮጵያ ዘርፍ ምክር ቤትን ለስምንት ዓመታት በፕሬዚዳንትነት የመሩት አቶ ገብረህይወት ገብረእግዚአብሔር፣ የዘርፍ ምክር ቤቱ ነሐሴ 2008 ዓ.ም. ባካሔደው ጠቅላላ ጉባዔና ምርጫ በድጋሚ መመረጣቸው አግባብ አይደለም ተብሎ ተቃውሞ ቀርቦባቸው ነበር፡፡ በዘርፍ ምክር ቤቱ መተዳደሪያ ደንብ መሠረት ከሁለት የምርጫ ዘመን በላይ ማገልገል እንደማይቻል እየታወቀ፣ በድጋሚ ስለተመረጡ የሕግ ጥሰት ፈጽመዋል ተብለዋል፡፡ ይህ አቤቱታ ለኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ቢቀርብም እስከቅርብ ጊዜ ድረስ ምላሽ ሳይሰጥበት ቆይቷል፡፡ የአማራ ንግድ ምክር ቤት ፕሬዚዳንትም ከሁለት ጊዜ በላይ መመረጥ እንደማይችሉ እየታወቀ የተመረጡ ስለሆነ፣ ይህም የሕግ ጥሰት ሆኖ ሲያከራክር ቆይቷል፡፡
የአዲስ አበባ ዘርፍ ምክር ቤትም ከኢትዮጵያው ምክር ቤት ጉባዔ በፊት ምርጫ ማድረግ ሲገባው፣ ይህንን ሳያደርግና ያለ ምርጫ ውክልና የዘርፍ ምክር ቤቱ አባል እንዲሆኑ አድርጓቸዋል የተባሉት አቶ አበባው መኮንን ናቸው፡፡ አቶ አበባው አሁን የሥልጣን ዘመኑን ያጠቃለለው የኢትዮጵያ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ምክትል ፕሬዚዳንት፣ እንዲሁም በቅርቡ በተደረገ ምርጫ የአዲስ አበባ ንግና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ምክትል ፕሬዚዳንት ሆነው ለሁለተኛ ጊዜ እንደተመረጡ አይዘነጋም፡፡ እነዚህ ለንግድ ሚኒስቴር በይፋ ተቃውሞ የቀረበባቸው ጉዳዮች ሲሆኑ፣ ምርመራ የሚሹ ሌሎችም የሕግ ጥሰቶች እንዳሉ በመጥቀስ ሚኒስቴሩ ሊያጣራ ይገባል ተብሏል፡፡ እንወክለዋን ወይም እንመራዋለን የሚሉትን የንግድ ኅብረተሰብ ጉዳይ እርግፍ አድርገው ትተው ዋነኛ አጀንዳቸው በምርጫው ላይ ብቻ ማድረጋቸው አመራሮቹን ጥያቄ ውስጥ እንደከተታቸው አባላት እየገለጹ ይገኛሉ፡፡
ድምፅ መግዣ አባላት
በአጣሪ ግብረ ኃይሉ ይጣሩ ተብለው ከተለዩ ጉዳዮች መካከል አባል ምክር ቤቶች ስንት አባላት አሏቸው የሚለው ይገኝበታል፡፡ በኢትዮጵያ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት በአባልነት የታቀፉት 18ቱ ንግድ ምክር ቤቶች ከ500 ሺሕ በላይ አባላት እንዳሏቸው ይነገራል፡፡
የእያንዳንዱ ንግድ ምክር ቤት አባላት ብዛት ምን ያህል እንደሆነ ለማወቅ ይፈተሽ ተብሎ ሲጣራ የተገኘው ውጤት ግን ከላይ ከተጠቀሰው ቁጥር ያነሱ አባላት መኖራቸው ነው፡፡ ከ100 ሺሕ በላይ በአባልነት የተመዘገቡ ሰዎች፣ አባልነታቸውን የሚያረጋግጥ ማስረጃ ሊቀርቡ አልቻሉም፡፡ ምክር ቤቶቹ እንዲያቀርቡ ተጠይቀውም ሊሆን አልቻለም፡፡ ይህ ጉዳይ በንግድ ሚኒስቴር የማጣራት ሥራ ወቅት ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባ ያመለከቱ በርካቶች ነበሩ፡፡
ለዓመታት በሕጋዊ ሆነ በሕገወጥ የምርጫ ሒደት ኃላፊነቱን ይዘው የቆዩ ግለሰቦች በሥልጣን ላይ ለመቆየት ባላቸው ፍላጎት ሳቢያ ንግድ ምክር ቤቶችን ለመምራት አቅም ያላቸው አባላት እንዳይወጡ በሩን ስለዘጉ፣ ከዚህ በኋላ እንዲህ ያለው አሠራር እንዳይቀጥል ተጠይቋል፡፡ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ የኢትዮጵያ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤትን የአመራር ቦታ ለማግኘት እያንዳንዱ አባል ለምርጫ የሚኖረው ድምፅ የአባላትን ቁጥር መሠረት በማድረግ በሚሠራ ቀመር ይሁን ተብሏል፡፡
የበለጠ ድምፅ ለማግኘት ተመሳሳይ ዓላማ ያላቸውን የሌሎች ንግድና ዘርፍ ምክር ቤቶችን አመራሮች በመያዝ አንተ ለእኔ እከሌ ላንተ ድምፅ እንስጥ ተባብለው በመቧደን፣ በያዙት ሕገወጥ ድምፅ ከምርጫ በፊት የኃላፊነት ቦታዎችን ለየራሳቸው ደልድለው ወደ ምርጫ የሚገቡ እንዳሉም ተጠቅሷል፡፡ እንደ ምንጮች ገለጻ ንግድ ሚኒስቴር ጠቅላላ ጉባዔው እንዲዘገይ ከመወሰኑ ጥቂት ቀናት ቀደም ብሎ ጥቂት ግለሰቦች እርስ በርሳቸው ተመራርጠው፣ የምርጫውን ዕለት ሲጠባበቁ ነበር መባሉን በምሳሌነት ያነሳሉ፡፡
ማን ፕሬዚዳንት? ማን ምክትል ፕሬዚዳንት? እንደሆነ እነማንስ የቦርድ አባላት ይሁኑ በሚለው ላይ ተስማምተው እንደነበር የሚገልጹት ምንጮች፣ ንግድ ምክር ቤቱን ለመምራት የሚጣደፉ ወገኖች ሕገወጥነት ምን ያህል አስቸጋሪ እየሆነ እንደመጣ ይጠቅሳሉ፡፡ ንግድ ሚኒስቴር ይህንን ጉዳይ በማጣራት ውሳኔ ለመስጠትና እንዲሁም ከዚህ በኋላ ተመሳሳይ ነገር እንዳይፈጸም የሚያደርግ አሠራር እንዲኖር ከፈለገ ጉዳዩን የሚያጣሩት ባለሙያዎች ጠንካራ ሊሆኑ እንደሚገባቸውም እየመከሩ ነው፡፡
በቅርቡ በኢትዮጵያ ዘርፍ ምክር ቤት ለተፈጠረው ያለመግባባት ውዝግብ አንዱ መነሻ የምክር ቤቱ መተዳደሪያ ደንብ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ጠቅላላ ጉባዔ ከማካሄዱ በፊት የኢትዮጵያ ዘርፍ ምክር ቤት ጠቅላላ ጉባዔ ማድረግ ይጠበቅበት ነበር፡፡ በነሐሴ 2008 ዓ.ም. ጠቅላላ ጉባዔውንና ምርጫውን ሳያካሂድ፣ ይልቁንም ከ1999 ዓ.ም. ጀምሮ ሲሠራበት ቆይቷል የተባለውን መተዳደሪያ ደንብ በነሐሴ 2008 ዓ.ም. ጠቅላላ ጉባዔ ላይ ፕሬዚዳንትና ጸሐፊው ተሻሻለ የተባለውን ረቂቅ ደንብ ያፅድቅልን በማለት ማቅረባቸው አይዘነጋም፡፡
በወቅቱ ተሻሻለ የተባለው ደንብ ቀድሞ አባል ምክር ቤቶች ሳይወያዩበት፣ ረቂቁም ሳይደርሳቸው አፅድቁልን ብለው በመምጣታቸው የደቡብ ክልል ዘርፍ ምክር ቤት ተወካዮች ተቃውመውት እንደነበር አይዘነጋም፡፡ ጠቅላላ ጉባዔውን ረግጠው ለመውጣት ምክንያት እንደሆናቸውም ይታወሳል፡፡
ተሻሽሎ ቀረበ የተባለው መተዳደሪያ ደንብም አሻሻለ የተባለው ነጥብና የተሻሻለበት ምክንያት ምን እንደነበር በግልጽ መታየቱ ይታወሳል፡፡ በ1999 ዓ.ም. የፀደቀውና ሲሠራበት የቆየው ደንብ ውስጥ ዘርፍ ምክር ቤቱን የሚመሩ ሰዎች የሥልጣን ዘመንን ገድቦ ቆይቷል፡፡ አንድ ተመራጭ ለሁለት የሥልጣን ዘመን ወይም ለአራት ዓመታት ብቻ ማገልገል እንደሚችል ያስቀምጣል፡፡ ተሻሽሏል ተብሎ እንዲፀድቅ በቀረበው መተዳደሪያ ደንብ ውስጥ ግን የሥልጣን ዘመንን የሚገድበውን አንቀጽ እንዲወጣ መደረጉ የተመራጮች የሥልጣን ዘመን ሳይገደብ እንዲቆዩ የሚፈቅድ ሆኖ ተገኝቷል፡፡ ይህ በመሆኑ በወቅቱ ፕሬዚዳንቱን ጨምሮ ዘጠኝ የቦርድ አባላት ሕግ ከሚፈቅድላቸው በላይ በድጋሚ ለመመረጥ ያደረጉት ነው በማለት የደቡብ ዘርፍ ምክር ቤት ተቃውሞታል፡፡ የዘርፍ ምክር ቤቱ ፕሬዚዳንት ስምንተኛ ዓመታቸውን ይዘዋል፡፡ ይህ በመሆኑም ለመንግሥት አቤቱታ ቀርቦበታል፡፡
የኢትዮጵያ ንግድ ምክር ቤት በ2008 ዓ.ም. በተደረገ ወደ አመራር ለመምጣት የሚደረገውን ጥረት ለማስቀረት አንድ ተመራጭ የሥልጣን ገደቡ እንዲገደብ የሚያደርገው የተሻሻለ ደንብ ደግሞ ከብዙዎች አባል ምክር ቤቶች ተቀባይነት ያለማግኘቱ ነው፡፡ በቅርቡ የተፈጠረውን ውዝግብ ሲያጣራ የነበረው አጣሪ ኮሚሽን አባል ምክር ቤቶች እንዲህ ያሉትን አንቀጾችም የተሻሻለውን መተዳደሪያ ደንብ አልተቀበሉትም ይሻሻል ብለዋል፡፡ ይህ ግን የሚያመላክተው ደጋግሞ ሊመረጥ ከመፈለግ የተነሳ ነው በሚል ሲተች ነበር፡፡