የኢትዮጵያ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤትን በፕሬዚዳንትነት፣ በምክትል ፕሬዚዳንትና በቦርድ አባልነት ለማገልገል የሚችሉ ኃለፊዎችን ለመሰየም በየሁለት ዓመቱ ምርጫ ይካሄዳል፡፡ ይሁን እንጂ ምርጫው በሚካሄድባቸው ጊዜዎች የሚነሳው ውዝግብ እየተለመደ ከመጣ ከጀመረ ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡ ያለጭቅጭቅና ትርምስ የተካሄደ ምርጫ ማየት ዘበት እየሆነ መጥቷል፡፡
ንግድ ምክር ቤቶች በየጊዜው ተተኪና ጠንካራ አመራር ለምን አይኖራቸውም? የሚል ትችት እንዲነሳባቸው ምክንያቶች ከሆኑት አንዱ በውዝግብ መሃል ወደ አመራር ቦታው ደጋግመው የሚጡ ግለሰቦች ሳይወጡ ለዓመታት የሚጥኝ ብለው መንበራቸውን በመያዛቸው ነው፡፡ ለዚህ ወቀሳ ተጋላጭ አነጋጋሪ የሆነው ኢትዮጵያ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ነው፡፡
አመራሮቹ አንዴ የክልል ወይም የከተማ ንግድና ዘርፍ ምክር ቤት አመራር ቦታውን ይዘው ቆይተው ሲበቃጨው ደግም በሌላ የምርጫ ዘመን ወደ አገር አቀፉ ምክር ቤት በመምጣት ለዓመታት እየተፈራረቁ ቦታውን ይዘዋል መባሉ፣ በንግድ ምክር ቤቱ ይሄ ነው የሚባል የአመራሮች ለውጥ እንዳይታይ አድርጓል፡፡ ይህ መሆኑም ውዝግብ ውስጥ እንዲዘፈቅ እንዳስገደደው ሲተች ቢቆይም፣ አሁንም ከገባበት አዙሪት ሊወጣ አልቻለም፡፡ ይህንን ገጽታ ለመለወጥ የሚደረጉ ጥረቶችም ቢሆኑ፣ እክል ሲገጥማቸው መታየቱ ንግድ ምክር ቤቱ ላይ አሉታዊ ገጽታ አሳድሯል፡፡
በአሁኑ ወቅት በአመራር ቦታ ላይ ያለው የንግድ ምክር ቤቱ ቦርድም የሁለት ዓመት የሥልጣን ዘመኑ አብቅቷል፡፡ ይሁንና ጠቅላላ ጉባዔ ጠርቶ ምርጫ በማካሄድ ኃላፊነቱን ለማስረከብ እንዳልቻለ መግለጹ፣ የንግድ ምክር ቤቱን ችግር አሳይቷል፡፡ በሕግና በመተዳደርያ ደንብ በተቀመጠው አግባብ መሠረት፣ ጠቅላላ ጉባዔ ጠርቶ ወቅቱን ጠብቆ ምርጫ ያለማካሄዱ ዋነኛ ምክንያትም ከምርጫ ሥርዓት የሚነሱ ውዝግቦች ያሳደሩትና ለዓመታት ያልተፈታ ችግር ነው፡፡ የንግድ ምክር ቤቱ ቦርድ ጠቅላላ ጉባዔ አካሂዶ ኃላፊነቱን ማስረከብ ሲገባው፣ ለወራት የዘገየው ሕጋዊ አካሄዶችን ጥያቄ ውስጥ የሚከቱ ችግሮች እንደገጠሙት እንደሆነ ማስታወቁ ይታወሳል፡፡ ማሳወቅ ብቻም ሳይሆን ስምንተኛውን ጠቅላላ ጉባዔ ለማካሄድ እንዳልችል እክል ሆነዋል ያላቸውችግሮች ለመፍታት 18ቱን አባል ንግድ ምክር ቤቶች ለመፍትሔ ውይይት ለመጥራት ተገዷል፡፡ አባል ምክር ቤቶቹ አጋጥመዋል የተባሉትን ችግሮች የሚፈትሽና ውሳኔ የሚሰጥ እንዲሁም፤ የዘገየውን ጠቅላላ ጉባዔ ለመጥራትና ምርጫ ለማካሄድ የሚያስችል ሰባት አባላት የተካተቱበት ግብረ ኃይል አቋቁመዋል፡፡ ግብረ ኃይሉም ለሁለት ወራት ጉዳዩን ሲመረምር ቆይቶ፣ የደረሰበትን ድምዳሜና የውሳኔ ሐሳብ ለ18ቱም የምክር ቤቶች መሪዎች፣ ባለፈው ሳምንት መጀመሪያ ላይ ይፋ አድርጓል፡፡
ምክር ቤቱን ያጋጠሙት ችግሮች
የኢትዮጵያ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ቦርድ አመራር፣ ጠቅላላ ጉባዔውን እንዳያካሂድ እንቅፋት ሆነዋል በማለት ካቀረባቸው ችግሮች መካከል ከንግድ ምክር ቤቶች የማቋቋሚያ አዋጅ ውጭ አባል ምክር ቤቶች ምርጫ አካሂደዋል መባሉ ነው፡፡ ምክር ቤቶቹ በአግባቡ ምርጫ ሳያካሂዱ ወደ ላይኛው እርከን ተወካይ አመራሮችን ከላኩ የሕግ ጥሰት ስለሚያስከትል፣ ጉዳዩ እንዲጣራለት በመፈለጉ ነው፡፡ ይህንኑ የተመለከቱ ቅሬታዎች ከተለያዩ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤቶች መቅረባቸውንም አስረድቷል፡፡ የሥር ንግድ ምክር ቤቶች ሳይወክሏቸው ወደ ላይኛው እርከን የመጡ አመራሮች መኖራቸውን የሚያሳዩ ቅሬታዎች በመቅረባቸው፣ ይህ ቅሬታ ሳይፈታ የብሔራዊ ንግድ ምክር ቤቱን ጠቅላላ ጉባዔ ማካሄድ ችግር ሆኖብኛል ማለቱ ተጠቅሷል፡፡ ይህንና ሌሎችም ችግሮችን እንዲያጣራ የተሰየመው አጣሪ ኮሚቴ፣ ለሁለት ወራት ያደረገውን የማጣራት ሥራ አጠናቆ ሰኞ ዕለት፣ ታኅሳስ 23 ቀን 2009 ዓ.ም. ውሳኔ አዘል ሪፖርቱን አሰምቷል፡፡
የግብረ ኃይሉ ሪፖርት
የግብረ ኃይሉ ሰብሳቢና የትግራይ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ፕሬዚዳንት አቶ አሰፋ ገብረሥላሴ በሪፖርታቸው እንደጠቆሙት፣ ውሳኔ ሊሰጥባቸው ይገባል ተብለው የታመነባቸውን ጉዳዮች በመለየት በሰባት ዋና ዋና ጉዳዮች ላይ ውሳኔ ተላልፏል፡፡ በተለይ ስምንተኛውን ጠቅላላ ጉባዔ ለመጥራት የሚያስችልና ወደፊት የሚመረተው አዲስ አመራርም ኃላፊነቱን ከተረከበ በኋላ ሊተገብራቸው ይገባል የተባሉ ሐሳቦችም የተካተቱበት ነው፡፡ ለንግድ ምክር ቤቱ የውዝግብ ምንጭ የሆኑ ጉዳዮች ላይ የደረሰበትን ውሳኔም ግብረ ኃይሉን ለሰየሙት ለ18ቱ አባል ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤቶች አሰምቷል፡፡
በአባል ምክር ቤቶች ቀረቡ የተባሉ ቅሬታዎችን በዝርዝር እንደፈተሸ የጠቀሰው ግብረ ኃይሉ፣ የቀረቡት ቅሬታዎች ሙሉ በሙሉ የሕግ ጥሰት ተፈጽሟል የሚል ክስ ያስተናገዱ ክሶች ሆነ ተገኝተዋል፡፡ አብዛኞቹም የምርጫ ሥነ ሥርዓት ግድፈት፣ የአወካከልና የደንብ ጥሰት ቅሬታዎች እንደነበሩ ተጠቅሷል፡፡ ግብረ ኃይሉ የቀሩበለትን ቅሬታዎች ለመፍታት የሚያችሉ መረጃዎችን ሰብስቦ ለማጣራት ረዥም ጊዜ የሚጠይቅና የሕግ ምክርም የሚያሻው ሥራ ቢሆንምበትም፣ ከሕግ አኳያ ባሉ ጉዳዮች ላይ ተንተርሶ ፍተሻ በማድረግ ከውሳኔ ላይ እንደደረሰ ይፋ አድርጓል፡፡
እያንዳንዱ አባል ምክር ቤት በአዋጁ መሠረት በዓመት አንድ ጊዜ ጠቅላላ ጉባዔውን፣ በየሁለት ዓመቱም ምርጫ ማካሄድና ለጠቅላላ ጉባዔ የኦዲት ሪፖርት ማቅረቡ ተረጋግጦ ለኢትዮጵያ ምክር ቤት ጉባዔ ዕጩ ማቅረብ አለበት የሚል ድምዳሜ ላይ ደርሷል፡፡ አባል ምክር ቤቶች ከታች እስከ ላይ አባሎቻቸውን ያሳተፈ ጉባዔ ማካሄዳቸው ተረጋግጦ፣ ለጠቅላላ ጉባዔ እንዲቀርቡና ምክር ቤቶቹም ለሕግ ተገዥ በመሆን ግዴታቸውን እንዲወጡ በማለት ወስኗል፡፡
በሚደረገው የማጣራት ሒደት ሕጉን ያሟሉ ብቻ ለጠቅላላ ጉባዔ እንዲቀርቡ፣ በተለይም ከታች ጀምሮ አሳታፊ በሆነ የምርጫ ሥነ ሥርዓት እንዲካሄድ ያሳሰበው ግብረ ኃይሉ፣ ከታች ምክር ቤት ሳይወከሉ ለላይኛው ምክር ቤት ውክልና የቀረቡ አባላት ካሉ የሕግ ጥሰት እየፈጸሙ መሆናቸውን አውቀው እንዲያስተካክሉ በማድረግ የአገር አቀፉ ምክር ምርጫ መካሄድ እንደሚችል ውሳኔውን አሳውቋል፡፡
በአጠቃላይ ሕግ መመርያና ደንብ የጣሰ የምርጫ ሒደት ካለ የኢትዮጵያ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ጽሕፈት ቤት የማጣራት ኃላፊነቱን ወስዶ ለጉባዔ ዝግጁ እንዲያደርግ በማለት ግብረ ኃይሉ ያቀረበው የውሳኔ ሐሳብ በ18ቱ ንግድ ምክር ቤቶች ተቀባይነት አግኝቷል፡፡ በዚሁ መሠረት ኃላፊነቱ አሁን ያለው ቦርድ ወስዶ በማጣራት ውሳኔ እንዲሰጥበት ተወስኗል፡፡
በዝርዝር ከቀረቡት የግብረ ኃይሉ ውሳኔዎች ውስጥ ሕጋዊ ንግድ ፈቃድ የሌለው ነጋዴ ከአባልነት እንዲሰረዝ፣ ሕጋዊ ሠርተፍኬት የሌለው ከተማ፣ ወረዳና ክልልም እንዲሁ ከአባልነት እንዲሰረዝ የሚሉት ይገኙበታል፡፡ ይህ የግብረ ኃይሉ ውሳኔ አባል የንግድና የዘርፍ ምክር ቤቶች በአባልነት የሚያቀርቧቸውን የአባላት ቁጥር ለማጥራት እንደሚያስችል ታምኖበታል፡፡
አቶ አሰፋ እንደጠቀሱትም፣ ግብረ ኃይሉ በዚህ ጉዳይ ላይ ያሳለፈው ውሳኔ አዋጁን መሠረት በማድረግ፣ ጉባዔው እንዲካሄድና የሕግ ልዕልናን በማረጋገጥ ፍትሐዊ ምርጫ ይካሄዳል በሚል እምነት ነው፡፡ በንግድ ምክር ቤቱ አዋጅ መሠረት ሊያሟሉ ይገባቸዋል ተብለው የተቀመጡ መሥፈርቶችን ስለማሟላታቸው በተደረገ የማጣራት ሥራም የአንድ ክልል ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት እስከ ቅርብ ጊዜ የምዝገባ ሠርተፍኬት ሳይኖረው ሲመርጥና ሲያስመርጥ መቆየቱነ እንደረጋገጠበት ገልጸዋል፡፡ በግብረ ኃይሉ ሪፖርት መሠረት የምዝገባ ሰርተፍኬት ሳይኖረው ሲመርጥና ሲመረጥ ቆይቷል የተባለው የሶማሌ ክልል ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ነው፡፡ ለዚህ ግድፈት የኢትዮጵያ ንግድ ምክር ቤት ተጠያቂ እንደሆነ ግብረ ኃይሉ አስታውቋል፡፡
በመጪው ምርጫ ግን አባል ምክር ቤቶች የምዝገባ ሰርተፍኬታቸው ታይቶና ሕጋዊነታቸው ተረጋግጦ እንዲሳተፉ የማድረጉ አሠራር በሕጉ መሠረት እንዲፈጸም ለምክር ቤቱ ጽሕፈት ቤት መመርያ አስተላልፎ ተግባራዊ እንደተደረገ ግብረ ኃይሉ ጠቅሷል፡፡
የተሻሻለው መተዳደርያ ደንብና የሚቀርፋቸው ቅሬታዎች
በግብረ ኃይሉ ውሳኔ ከተላለፈባቸው መካከል መስከረም 6 ቀን 2008 ዓ.ም. ተሻሽሎ የፀደቀው የንግድ ምክር ቤቱን መተዳደርያ ደንብን የሚመለከተው ይገኝበታል፡፡ ተሻሻለ የተባለው መተዳደርያ ደንብ በአባል ምክር ቤቶች በኩል በርካታ ቅሬታዎችን ያስነሳ በመሆኑ፣ በምክር ቤቶች በኩል ለመተባበር የሚያስችል ተጨባጭ ሁኔታ አለመታየቱን የግብረ ኃይሉ ሪፖርት ይገልጻል፡፡ ለጭቅጭቅም ዋነኛ መንስዔ ሊሆን ችሏል፡፡ ከተሻሻለው መተዳደሪያ ደንብ ውስጥ ከ18 አባል ምክር ቤቶች 12ቱ በተለይ የአባልነት መዋጮን የተመለከተውን አንቀጽ አልተቀበሉትም፡፡ መተዳደርያ ደንቡ ሲፀድቅም፣ በምክር ቤቱ አባላት በቂ ውይይት እንዳልተደረገበት በተለያዩ አጋጣሚዎች በመግለጽ፣ በሥራ ላይ ያለው ቦርድም በዚህ ጉዳይ ላይ መግባባት ላይ መድረስ ስላልቻለ የመተዳደርያ ደንቡ ድጋሚ ለጠቅላላ ጉባዔ ቀርቦ እንዲሻሻል ውሳኔ አሳልፏል፡፡
አምስት ብር ሲያከራክር
በስብሰባ ወቅት የአባል ንግድ ምክር ቤቶችን አመራሮችና የግብረ ኃይሉን አባላት ካፋጩና ረጅም ጊዜ ከወሰዱ ጉዳዮች መካከል አንዱ 18ቱ አባል ምክር ቤቶች ለኢትዮጵያ ንግድ ምክር ቤት የሚየደርጉት ዓመታዊ መወጮ ምን ያህል ይሁን የሚለው ነበር፡፡
በተሻሻለው መተዳደርያ ደንብ ውስጥ 18ቱ አባል ምክር
ቤቶች በየዓመቱ በየአንዳንዱ ግለሰብ አባል 5 ብር እንዲያዋጡ ይጠይቃል፡፡ ይህ ክፍያ በዝቷል ተብሎ ወደ ሁለት ብር ዝቅ ይበል የለም ሦስት ብር ይሁን የሚለው ኃሳብ ሲያሟግት ውሏል፡፡ በአንድ ነጋዴ አባል ይህንን የአምስት ብር ዓመታዊ ክፍያ ለመክፈል አይቻለንም የሚለው ሐሳብ ረዥም ጊዜ ወስዶ ማከራከሩ አስገራሚ ነበር፡፡
ግድ የለም በአንድ አባል ሦስት ብር መዋጮ ይከፈል የሚለው የግብረ ኃይሉን ውሳኔ ለመቀበል ብዙ ማነታረኩ ብቻም ሳይሆን ይህንንም ማሟላት በማይቻልበት ወቅት በዱቤ እንድንከፍል ታሳቢ ይደረግለት ሲሉም ተደምጠዋል፡፡ በመጨረሻው ግን በእያንዳንዱ አባል ሦስት ብር መዋጮ ይደረግ በሚለው ሐሳብ ላይ ድምፅ ተሰጥቶ ተቋጭቷል፡፡ አንድ ነጋዴ በአባልነቱ በዓመት አምስት ብር እንዲያዋጣ ለማድረግ ይህንን ያህል ከባድና አከራካሪ የመሆኑ ጉዳይ እንቆቅልሽ መሆኑ ግን አልቀረም፡፡
ይህንን ጉዳይ በተመለከተ ግብረ ኃይሉ 18ቱ አባል ምክር ቤቶች ባለባቸው የተጣራ አባል ልክ ተሰልቶ ለአንድ አባል ሦስት ብር፣ ለነባርና ለአዲስ ማስመዝገቢያ አምስት ብር እንዲከፍሉ ተብሎ የነበረው በሦስት ወር እንዲሻሻል የውሳኔ ሐሳብ አቅርቧል፡፡ ከዚህ ቀደም የከፈሉ ካሉም ለወደፊቱ እንዲታሰብላቸው፣ እስካሁን ያልከፈሉ ግን በተጣራ የአባል ቁጥራቸው ልክ የሦስት ብር ዕዳ ተመዝግቦባቸው በሰነድ ተፈርሞ ወደፊት እንዲከፍሉ ግብረ ኃይሉ ያቀረበው የውሳኔ ሐሳብ ድምፅ ተሰጥቶበት ተወስኗል፡፡
የምርጫ ውክልና
ግብረ ኃይሉ ከ18ቱ አባል ምክር ቤቶች በአገር አቀፉ ጠቅላላ ጉባዔ የሚወከሉ አባላት ቁጥር ስንት ይሁን በሚለው ነጥብ ላይ ያቀረበው የውሳኔ ሐሳብ ተቀባይነት አግኝቷል፡፡ በቀጥታ የሚወከሉ የዘርፍ አባላትና አነስተኛ ቁጥር ላላቸው ክልሎች በሥራ አመራር ቦርድ ምርጫ መሳተፍ እንዳለባቸው በተመለከተው አጀንዳ ውስጥ፣ አነስተኛ የአባላት ቁጥር ያላቸው ክልሎችም ይህን ጥያቄ የሚያነሱ በመሆኑ ግብረ ኃይሉ በዚህ ላይ ውሳኔ ሰጥቷል፡፡
እየተሠራበት ያለው የሥራ አመራር ቦርድ ዕጩ አቀራረብ ሥርዓት ፍትሐዊ ስላልሆነ፣ የዕጩ አቀራረብ ሥርዓቱ ማስተካከያ እንዲደረግበት ግብረ ኃይሉ መወሰኑን የገለጹት አቶ አሰፋ፣ ከሥራ አመራር ድልድል እስከ ፕሬዚዳንትነት ወይም ምክትል ፕሬዚዳንትነት ቦታ ያሉት ኃላፊነቶች ላይ አማራጭ ሐሳቦች የቀረቡ ቢሆንም ለምርጫ ሥርዓቱና ለዴሞክራሲያዊ ሒደቱ አሠራር አስቸጋሪ በመሆናቸው እስካሁን የነበረው የሥራ አመራር ቦርድ የዕጩ አቀራረብ ሒደት እንዲለወጥ አድርጓል፡፡ ከዚህ ቀደም እያንዳንዱ አባል ምክር ቤት 11 ዕጩዎችን የማቅረብ ዕድል ነበረው፡፡ ይህም በብዛት ዕጩ ያቀረቡ ክልሎች ብቻ ብዙ የማስመረጥ ዕድል እንዲገኙ የሚያደረግ እንደነበር አስታውሰዋል፡፡ አገራዊ ምክር ቤቱ በተወሰኑ ተመራጮች ብቻ እንዳይያዝ፣ ውክልናውም ፍትሐዊ እንዲሆን በማሰብ የውክልና ቁጥሩ መቀየሩን ግብረ ኃይሉ አስታውቋል፡፡
በዚህ መሠረት የ18ቱ አባል ምክር ቤቶች የተለያየ ቁጥር የአባላት ብዛት ቢኖራቸውም በአባል ቁጥራቸው ድምፅ የመስጠት መብት እንደተጠበቀ ሆኖ ለአገራዊ ምክር ቤቱ ለምርጫ ውድድር ግን ሁሉም አባል ምክር ቤቶች ሁለት፣ ሁለት ዕጩዎችን ብቻ እንዲያቀርቡ የቀረበው የውሳኔ ሐሳብ አስተያየቶች ከተሰጠበት በኋላ እንዲተገበር ተወስኗል፡፡ የሚቀርቡት ሁለት ዕጩዎች የሚወደደሩት ለፕሬዚዳንትነት ወይም ለምክትል ፕሬዚዳንትነት አለያም በሥራ አመራር ቦርዱ ውስጥ በአባልነት ለመሳተፍ እንደሚሆን አመልክቷል፡፡
በዚህ መሠረት ለፕሬዚዳንትነት የሚወዳደር ዕጩ፣ ለምክትል ፕሬዚዳንትነት ወይም ለቦርድ አባልነት መወዳደር አይችልም፡፡ ለምክትል ፕሬዚዳንትነት የሚወዳደረውም ለፕሬዚዳንትነት ወይም ለቦርድ አመራር ሊወዳደር አይችልም፡፡ ለሥራ አመራር ቦርድ አባልነት የሚወዳደረው እንደዚሁ፡፡ በመተዳደርያ ደንብ ቁጥር 02/2008 መሠረት ማንኛውም በሥራ አመራር ቦርድ፣ በፕሬዚዳንትነትና በምክትል ፕሬዚዳንትነት ያገለገለ አመራር፣ የአገልግሎት ዘመኑ ለሁለት ተከታታይ የምርጫ ጊዜ ብቻ እንዲሆን፣ ከሁለት ጊዜ ምርጫ በኋላ በድጋሚ መመረጥ የሚችለው ቢያንስ ከአንድ ቆይታ በኋላ እንዲሆን በማለት የቀረበውም ሐሳብም ተቀባይነት አግኝቷል፡፡
የአስመራጭ ኮሚቴ ተወግዷል
ግብረ ኃይሉ ባደረገው ማጣራት፣ ለንግድ ምክር ቤቱ ውዝግቦች በተለይም በምርጫ ወቅት ለሚፈጠሩ ጭቅጭቆች አንዱ መንስዔ ምርጫውን ለማስፈጸም ሲባል የሚቋቋመው የምርጫ አስተባባሪ ኮሚቴ ነው፡፡ የጠቅላላ ጉባዔውን ሒደት፣ ውክልና ቀመርና የምርጫ አፈጻጸም ሥርዓት ለምርጫ አስተባባሪ ኮሚቴ የተሰጠው የሥራ መዘርዝርና ኃላፊነት ችግር ስለነበረበት፣ የኮሚቴ አሠራር እንዲቀር ተብሏል፡፡ ለስምንተኛው ጠቅላላ ጉባዔ ዝግጅትም የምርጫ አስተባባሪ ኮሚቴ መኖሩ ጠቀሜታ እንደማይኖረው በመታመኑ የአስመራጭ ኮሚቴ አወቃቀር ይቅር የሚለው ሐሳብ ድምፅ ተሰጥቶበት አልፏል፡፡ ስለዚህ ኮሚቴው ቀርቶ ኮሚቴው ይሠራው የነበረውን ሥራ ጽሕፈት ቤቱ ተረክቦ፣ የሚቀርቡት ዕጩዎች መመዘኛውን ማሟላታቸውን በጥንቃቄ ፈትሾ እንዲያቀርባቸው ኃላፊነት ተሰጥቶታል፡፡
የውጭ ጉዞዎች
ንግድ ምክር ቤቱ በተደጋጋሚ የሚወቀስበት አንዱ ጉዳይ በአመራር ላይ ያሉ አባላት የሚያደርጓቸው የውጭ አገር ጉዞዎችን የሚመለከተው ነው፡፡ በግብረ ኃይሉ ሪፖርትም ይህ ጉዳይ ተካቷል፡፡ በዚህ ዙሪያ ያሉትን ጉዳዮች አጣርቻለሁ ያለው ግብረ ኃይሉ፣ ‹‹አገር አቀፍ ምክር ቤቱ የተለያየ የውጭ ጉዞ ፕሮግራሞች እንዳሉት ቢታወቅም፣ በተመራጭ ቦርዱም ይሁን በአባል ምክር ቤቶች ዘንድ የቅሬታ ምንጭ በመሆን ላይ ይገኛል፤›› ብሏል፡፡ ዋናው የግልጽነት ችግር መነሻ ተብሎም ይጠቀሳል፡፡ በመሆኑም የውጭ ጉዞዎች ግልጽነት እንዲኖራቸው፣ ፕሬዚዳንቶች ወይም ጸሐፊዎች የሚያደርጉት ጉዞም ለቦርዱ በማሳወቅ ሪፖርት የማቅረብ ግዴታ እንዲጣልባቸው ውሳኔ አሳልፏል፡፡ ከአባል ምክር ቤቶቹ ወደ ውጭ የሚላኩ ተወካዮች፣ አባል መሆናቸው ተረጋግጦ፣ ግልጽነትና ተጠያቂነት ያለበት የውጭ ጉዞ ፕሮግራም እንዲዘጋጅና በመተዳደሪያ በደንቡ ውስጥም እንዲካተት በማለት ግብረ ኃይሉ ያቀረበውን ሐሳብ ቤቱ ተቀብሎታል፡፡
የአገሪቱ የንግድ ምክር ቤቶች ምንም እንኳ በአዋጅ ተቋቋመው የግል ዘርፉን በማገልገል ላይ ቢገኙም የተጠበቀው ያህል እየተጓዙ አይደለም በማለት የግብረ ኃይሉ በሪፖርቱ ተችቷቸዋል፡፡ በአገሪቱ ዋነኛ የኢኮኖሚ አንቀሳቃሽ የሚባሉ ባለሀብቶችም ከማኅበራቱ እየራቁ መሆናቸውና ለዚህም ምክንያቱ ብዙውን ጊዜ በምርጫ ጊዜ የሚታዩ ሽኩቻዎችና በየደረጃቸው በተደጋጋሚ ለምርጫ የሚቀርቡ ተወዳዳሪዎች በመተካካት ቦታቸውን ስለማለቁ ነው በማለት ምልከታውን አስቀምጧል፡፡ ለዚህም የአደረጃጀቱ ወይም የአዋጁ በየጊዜው አለመፈተሽና የአወቃቀር ችግሮች እንደሚጠቀሱም አመላክቷል፡፡
ቀጣዩ ዕርምጃ
የ18ቱ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤቶች በስብሰባቸው ወቅት ግብረ ኃይሉ ባቀረባቸው የውሳኔ ሐሳቦች ላይ ከስምምነት ላይ የደረሱበትን ውሳኔ እንዲያተገብር ዋነኛ ኃላፊነት የተሰጠው ለቦርዱ ነው፡፡ በዕለቱ በተላለፈው ውሳኔ መሠረት፣ በተቀመጠው የሕግ አግባብ ያልተካሄደ ምርጫና ውክልና ካለ እስከማገድ የሚደርስ ኃላፊነት ተሰጥቶታል፡፡ ግብረ ኃይሉ በወሰነው መሠረት፣ መፈጸም ያለባቸው ጉዳዮች ተጠቃለው ጥር 30 ቀን 2009 ዓ.ም. አገር አቀፍ ምርጫ እንዲካሄድ ቀነ ገደብ አስቀምጧል፡፡