በደቡብ ክልል ከሚገኙ 14 አስተዳደራዊ ዞኖች መካከል የዳውሮ ዞን አንዱ ነው፡፡ የዳውሮ ዞን ከጂማ ዞን ጋር በጎጀብ ወንዝ፣ ከወላይታ ዞን ደግሞ በጊቤ (ኦሞ) ወንዞች ይዋሰናል፡፡
እነዚህ ሁለት ትላልቅ ወንዞች በዳውሮ ምድር ላይ ተቀላቅለውና ኦሞ ወንዝ የሚል ስያሜ አግኝተው በኢትዮጵያና በኬንያ ድንበር ላይ ወደሚገኘው ቱርካና (ሩዶልፍ) ኃይቅ ይፈሳሉ፡፡
በእነዚህ ሁለት ትላልቅ ወንዞች ላይ ተሽከርካሪዎችን የሚያስተላልፉ ድልድዮች ቀደም ባሉት ጊዜያት ባለመገንባታቸው ዞኑ ለበርካታ ዓመታት ከሌሎች አጎራባች አካባቢዎች ተገልሎ እንደቆየ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡
ዘግይቶም ቢሆን በሁለቱ ወንዞች ላይ ተሽከርካሪዎችን የሚያስተላልፉ ድልድዮች ቢገነቡም፣ የዳውሮ ዞንን ከጂማም ሆነ ከወላይታ ዞኖች ጋር የሚያገናኙ መንገዶች ባለመገንባታቸው ዞኑ ከአጎራባች አካባቢዎች ጋር የሚገናኘው በጋማ ከብቶች፣ በእግር ጉዞና በአውሮፕላን ነበር፡፡
ወታደራዊው ደርግ ከመውደቁ ሁለት ዓመት ቀደም ብሎ በ1981 ዓ.ም. የዞኑ ተወላጅ የሆኑት አቶ በለጠ ባሹ የዳውሮ ገዥ ሆነው ተሾሙ፡፡ በአሁኑ ወቅት የ64 ዓመት የዕድሜ ባለፀጋና የአገር ሽማግሌ የሆኑት አቶ በለጠ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ በብዙ ውጣ ውረድ በወቅቱ ከነበረው የሰሜን ኦሞ አስተዳደር ዶዘርና ግሬደር በውሰት በመውሰድ ወላይታን ከዳውሮ የሚያገናኝ መንገድ አስጠርገዋል፡፡ ይህ መንገድ በ1982 ዓ.ም. ተመርቆ አገልግሎት መስጠት ጀመረ፡፡
በተመሳሳይም በምዕራብ አቅጣጫ ዳውሮን ከጂማ የሚያገናኝ መንገድም ጠረጋ ተካሂዷል፡፡ አቶ በለጠ እንደሚናገሩት እነዚህ መንገዶች በብዙ ድካም ከተከፈቱ በኋላ በወቅቱ ዳውሮ ውስጥ ተሽከርካሪ ያለው አንድም ሰው ባለመኖሩ ሌላ ችግር ነበር፡፡
‹‹የዳውሮ ዞን ተወላጅ የሆኑ አራት ባለሀብቶችን አስተባብሬ አንድ ላንድሮቨር ተሽከርካሪ አስገዝቼ ወደ መስመር አስገባሁ፤›› ሲሉ አቶ በለጠ ከ20 ዓመት በፊት የዳውሮ ዞን የነበረበትን አስቸጋሪ ሁኔታ ያስታውሳሉ፡፡
በዓባይ ወንዝ ላይ የሚገነባው ታላቁ የህዳሴ ግድብ እስኪጠናቀቅ ድረስ በኢትዮጵያ ትልቁ ሆኖ የሚቆየው የግልገል ጊቤ ሦስት ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክት በተለይ ለዳውሮና ለወላይታ ዞኖች ብዙ ለውጥ አምጥቷል፡፡ ይህ ፕሮጀክት 220 ኪሎ ሜትር መንገድ በሁለቱ ዞኖች ውስጥ ባሉ ወረዳዎች እንዲዘረጋ አድርጓል፡፡ በወላይታ ዞን መቀመጫ ሶዶ ከተማ እስከ ዳውሮ ዞን መቀመጫ ተርጫ ከተማ የአስፓልት መንገድ እንዲዘረጋ ምክንያት ሆኗል፡፡
ከ20 ዓመታት በፊት በመንገድ ጠረጋ ውጣ ውረድ ውስጥ ያለፉት አቶ በለጠ አሁን ያለው ለውጥ ተዓምር ሆኖባቸዋል፡፡ ‹‹በሕይወት እያለሁ ከሁሉም አካባቢዎች ኋላ ቀርቶ የቆየው ዳውሮ ዞን ብርሃን ሲፈነጥቅለት በመመልከቴ ፈጣሪን አመሰግናለሁ፤›› ይላሉ የዕድሜ ባለፀጋው አቶ በለጠ፡፡
ቅዳሜ ታኅሳስ 8 ቀን 2009 ዓ.ም. በይፋ ተመርቆ ሥራ የጀመረው የጊቤ ሦስት ኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫ ግድብ፣ ሐምሌ 1998 ዓ.ም. በወላይታና በዳውሮ ዞኖች ድንበር ላይ ነበር ግንባታው የተጀመረው፡፡ ከአዲስ አበባ በደቡብ ምዕራብ አቅጣጫ 450 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የሚገኘው ይህ ፕሮጀክት መጀመሩ ከዚህ ቀደም በጎጀብ ወንዝ ላይ ኃይል ማመንጫ ጣቢያ ይገነባል ተብሎ፣ ነገር ግን ይህ ዕቅዱ በመታጠፉ ለተቆጩ የዳውሮ ሕዝቦች ትልቅ የምሥራች ነበር፡፡
ይህ ግድብ 246 ሜትር ከፍታ ያለው ሲሆን፣ በአፍሪካም ሆነ በዓለም አቀፍ ደረጃ ከፍተኛ ቁመት ካላቸው ኃይል ማመንጫ ግድቦች ተርታ ይሰለፋል፡፡
‹‹በኮንክሪት ሙሌት (RCC) ቴክኖሎጂን በመጠቀም በዘመናዊ የምህንድስና ጥበብ የተገነባ ነው፤›› ሲሉ የግልገል ጊቤ ሦስት ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክት ሥራ አስኪያጅና የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ዋና ሥራ አስፈጻሚ ኢንጂነር አዜብ አስናቀ በምርቃቱ ወቅት ተናግረዋል፡፡
ይህ ግዙፍ ፕሮጀክት በአጠቃላይ አሥር ኃይል ማመንጫ ተርባይኖች ያሉት ሲሆን፣ እያንዳንዳቸው 187 ሜጋዋት፣ በድምሩ 1,870 ሜጋዋት ኤሌክትሪክ የማመንጨት አቅም አለው፡፡
ይህንን ግዙፍ ፕሮጀክት የሲቪል ሥራዎቹን የጣሊያኑ ሳሊኒ ኢምፕሬጂሎ አካሂዷል፡፡ በኢትዮጵያ ባለፉት ስድስት አሥርት ዓመታት በርካታ ግዙፍ ፕሮጀክቶችን ያካሄደው ሳሊኒ፣ የጊቤ ሦስትን ፕሮጀክት በስኬት አጠናቋል፡፡
የኤሌክትሮ ሜካኒካል ሥራዎችን የቻይናው ግዙፍ ኩባንያ ዶንግ ፉንግ ግሩፕ አክናውኖታል፡፡ የማማከር አገልግሎት የሰጡት የጣልያንና የፈረንሣይ ጥምር ኩባንያዎች የሆኑት ኢኤልሲ፣ ኤሌክትሮ፣ ኮንሰልትና ትራክተብል ኢንጂነሪንግ ናቸው፡፡ ከጊቤ ሦስት የሚመነጨው ኃይል የሚያስተላልፉና የሚያከፋፍሉ ፕሮጀክቶችን ደግሞ ቲቢኢኤ እና ሻንጋይ ኤሌክትሪክ ኩባንያዎች አካሂደዋል፡፡
ለኃይል ማመንጫ ግንባታው 1.5 ቢሊዮን ዩሮ ወጪ የተደረገ ሲሆን፣ ይህ ገንዘብ 60 በመቶ ከቻይና መንግሥት በተገኘ ብድር፣ 40 በመቶ ደግሞ በኢትዮጵያ መንግሥት ተሸፍኗል፡፡ የጊቤ ሦስት ፕሮጀክት በዳውሮና በወላይታ ዞን ውስጥ በርካታ መንገዶች እንዲገነቡ አድርጓል፡፡ በአጠቃላይም ከወላይታ ሶዶ ከተማ እስከ ኦሞ ድልድይ፣ ከኦሞ ድልድይ እስከ ዳውሮ ዞን ተርጫ ከተማ ድረስ ያለው መንገድ ግንባታ ተጀምሯል፡፡
የኢትዮጵያ መንገዶች ባለሥልጣን ሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ሳምሶን ወንድሙ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ይህ መንገድ በሁለት ምዕራፍ ተከፍሎ በአስፓልት ደረጃ እየተገነባ ነው፡፡ ግንባታውን ሁናን ሁንድ እና ቻይና ሬልዌይ ግሩፕ እያከናወኑ ይገኛሉ፡፡ ከዚህ ከዋናው የፌዴራል መንግሥት መንገድ ፕሮጀክት በተጨማሪ የሁለቱን ዞኖች ወረዳዎች የሚያገናኙ ከ220 ኪሎ ሜትር በላይ ርዝመት ያላቸው መንገዶች መገንባታቸው በወቅቱ ተገልጿል፡፡
በዳውሮ ዞን አምስት ወረዳዎችና አንድ የከተማ አስተዳደር ይገኛል፡፡ ግድቡ በፈጠረው ሐይቅ በተለይ በሁለቱ ወረዳዎች ውስጥ የሚገኙ 19 ቀበሌዎችን ይነካል፡፡
በወላይታ ዞን ደግሞ 12 ወረዳዎችና ሦስት የከተማ አስተዳደሮች ይገኛሉ፡፡ ሦስቱን ወረዳዎች ግድቡ የፈጠረው ሐይቅ ይነካል፡፡ በአጠቃላይ የጊቤ ሦስት ኃይል ማመንጫ ግድብና ግድቡ የፈጠረው ኃይልና አጠቃላይ ተፋሰስ (ካችመንት) 34,150 ካሬ ኪሎ ሜትር ስፋት አለው፡፡
የዳውሮ ዞን ፋይናንስና ኢኮኖሚ ልማት መምሪያ ኃላፊ አቶ ብርሃኑ ዳለቾ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ የጊቤ ሦስት ፕሮጀክት በመንገድ አውታር ዝርጋታ ለዞኑ ተወላጆች የሥራ ዕድል፣ የዓሣ ሀብትና ነፋሻ አየር አምጥቷል፡፡
‹‹ይህ ክስተት ትልቅ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታዎች አሉት፤›› ሲሉ ፕሮጀክቱ ያስገኘውን ጥቅም ገልጸዋል፡፡ ከዚህ ቀደም ይህ የኦሞ ሸለቆ በጣም ሞቃታማ ነበር፡፡ በሌሎች ዓመታት በተለይ ከኅዳርና ታኅሳስ ወር ጀምሮ ከብቶች የመኖ እጥረት ይገጥማቸዋል፡፡ ከዚህ በዘለለም በአካባቢው ምርታማነት የቀነሰ በመሆኑ፣ በሴፍቲኔት ፕሮግራም የታቀፈ አካባቢ ነው፡፡
አቶ ብርሃኑ እንደሚናገሩት የሐይቁ መፈጠር አካባቢው ነፋሻ አየር እንዲኖረው በማድረጉና መሬቱም እርጥበት እያገኘ በመሆኑ፣ ለግብርና ሥራ አመቺ ሁኔታ እየፈጠረ ነው፡፡ የዓሣ ሀብትም እንዲሁ ጥቅም ላይ መዋል ጀምሯል፡፡ ፕሮጀክቱ በርካታ ጀልባዎችንና የውኃ መሳቢያ ፓምፖችንም ለአካባቢው ማኅበረሰብ በማበርከቱ የተለያዩ ለውጦች እየመጡ መሆናቸውን አቶ ብርሃኑ ተናግረዋል፡፡
አቶ መስፍን ኩማ የወላይታ ዞን ዳሞት ሶሬ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ ናቸው፡፡ አቶ መስፍንም የአቶ ብርኑን ሐሳብ ይጋራሉ፡፡ አቶ መስፍን ለሪፖርተር እንደገለጹት ከዳውሮ ዞን ጋር በርካታ የሚጋሯቸውን ዕሴቶች ቢኖሩም፣ የመንገድ አውታር ባለመኖሩ ግንኙነታቸው ተገድቦ ቆይቷል፡፡
በአሁኑ ወቅት ግን በየብስ ብቻ ሳይሆን በጀልባ ጭምር መገናኘትና መገበያየት ጀምረዋል፡፡ ግድቡ የፈጠረው ሐይቅ ነፋሻ አየርና እርጥበት ይዞ በመምጣቱም በግብርና ሥራ ላይ መነቃቃት መፈጠሩን አቶ መስፍን ተናግረዋል፡፡
ይህ ግዙፍ ፕሮጀክት በመንገድ አውታር፣ በአየር ፀባይ ለውጥ፣ ለምግብ ዋስትና መረጋገጥ፣ ለሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነት፣ ለሥራ ዕድል ፈጠራ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ቢያበረክትም፣ አሁንም ግን በሁለቱም ዞኖች በርካታ አካባቢዎች ኤሌክትሪክ አቅርቦት እያገኙ አለመሆኑ ታይቷል፡፡ ጊቤ ሦስት በሙሉ አቅሙ ኢኮኖሚውን እየረዳ አለመሆኑም ታውቋል፡፡ ጊቤ ሦስት ኤሌክትሪክ ኃይል ግድቡ በተለይም ሁለቱ (ጊቤና ጎጀብን) ከምዕራብ ኢትዮጵያ ተራሮች የሚመነጩ ወንዞች በማግኘቱ ይህን አካባቢ የ2008 ድርቅ ያልነካው በመሆኑ በክረምቱ ወራትም በቂ ዝናብ በመኖሩ ግድቡ በቂ ውኃ ይዟል፡፡
እያንዳንዳቸው 187 ሜጋዋት የሚያመነጩት አሥሩ ተርባይኖች በሙሉ እንደሚሠሩ ተረጋግጧል፡፡ ነገር ግን ማመንጫ ጣቢያው በማመንጨት ላይ ያለው ኃይል ማመንጨት ከሚችለው በግማሽ ያነሰ (900 ሜጋዋት) ነው፡፡
የጊቤ ሦስት ኃይል ማመንጫ ኦፕሬሽን ኦፊሰር ቡድን መሪ አቶ ንጉሤ ማሙሻ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ አሥሩም ተርባይኖች ይሠራሉ፣ እያመነጨን የምንገኘው ግን 900 ሜጋዋት ኤሌክትሪክ ነው፡፡ ‹‹ይህንን ኤሌክትሪክ ተርባይኖቹን እየቀያየርን እናመርታለን፤›› ሲሉ አቶ ንጉሤ ተናግረዋል፡፡
‹‹የመሠረተ ልማቶች ተገንብተው ባለማለቃቸው ጣቢያው ማመንጨት የሚቻለውን በሙሉ ማመንጨት አልቻልንም፤›› ሲሉ አቶ ንጉሤ ገልጸዋል፡፡ የጊቤ ሦስት ኃይል መንጫ ጣቢያ የሚያመነጨውን ኃይል ለማስተላለፍና ለማሠራጨት የሚያስችሉ አውታሮች ተገንብተዋል፡፡ ከማመንጫ ጣቢያው እስከ ሶዶ ከተማ ከዚያም እስከ አዲስ አበባ ከተማ ድረስ 401 ኪሎ ሜትር ርዝመት የሚሸፍን ባለ 400 ኪሎ ቮልት ከፍተኛ የኃይል ማስተላለፊያ መስመር ተዘርግቷል፡፡ ከዚሁ ጋርም በሶዶና በአዲስ አበባ ከተማ 11 አዳዲስ ማከፋፈያ ጣቢያዎች ተገንብተዋል፡፡
መረጃዎች እንደሚጠቁሙት ግን የኤሌክትሪክ ፍላጎት ላላቸው ኢንዱስትሪዎች የእርሻ ፕሮጀክቶችና ወደመሳሰሉ ፕሮጀክቶች መስመሮችና ማከፋፈያዎች ባለመዘርጋታቸው ጊቤ ሦስት ማመንጨት ያለበትን ያህል እንዲያመነጭ አድርጎታል፡፡
የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ዋና ሥራ አስፈጻሚ ኢንጂነር አዜብ ለጋዜጠኞች እንደተናገሩት፣ ኃይል የማመንጨት አቅም አደገ ማለት ኤሌክትሪክ ለተጠቃሚው ማድረስ ተቻለ ማለት አይደለም፡፡
‹‹በመሀል ብዙ ነገሮች አሉ፤ ኤሌክትሪክ ማስተላለፊያ መስመሮች፣ ማሠራጫ ጣቢያዎች መኖር አለባቸው፡፡ እዚህ ጋ ጉድለት ካለ ማሠራጨት አይቻልም፡፡ እነዚህን መሠረተ ልማቶች ለማሟላት ጎን ለጎን እየሠራን ነው፤›› ሲሉ ኢንጂነር አዜብ ተናግረዋል፡፡
ኢትዮጵያን በታሪኳ ገጥሟት በማያውቅ ደረጃ ባለፈው 2008 ዓ.ም. ሰፊ ቦታ የሚሸፍን ድርቅ አጋጥሟት ነበር፡፡ ድርቁ የ10.2 ሚሊዮን ዜጎችን የምግብ ዋስትና ከማናጋቱ በላይ የኃይል ማመንጫ ግድቦች በቂ ውኃ መያዝ ባለመቻላቸው የኤሌክትሪክ አቅርቦት ጥያቄ ውስጥ ወድቆ ነበር፡፡
ነገር ግን ጊቤ ሦስት በወሳኝ ወቅት በመድረሱ ሊፈጠር የነበረውን የኤሌክትሪክ እጥረት የሸፈነ የቁርጥ ቀን ፕሮጀክት ሆኗል፡፡
ጊቤ ሦስት ኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክት የግንባታ ሒደት ግን አልጋ ባልጋ አልነበረም፡፡ ፕሮጀክቱ ከጥንስሱ ጀምሮ በርካታ ተቃውሞ የገጠመው ሲሆን፣ ተቃውሞው ጠንካራና ያልተቋረጠ ስለነበር ፕሮጀክቱን ፋይናንስ ለማድረግ ይሁንታ አሳይተው የነበሩ ዓለም አቀፍ ተቋማት ጭምር ቃላቸውን አጥፈዋል፡፡
ሳሊኒ ኮንስትራክሽን ሐምሌ 1998 ዓ.ም. አፈር ቆረጣ ሲጀምር በተለይ ኢንተርናሽናል ሪቨርስ ግሩፕና ኦክላንድ ኢንስቲትዩት ጊቤ ሦስት የአካባቢ ተፅዕኖ ግምገማ ያልተደረገለት ነው በሚል የታችኛው ተፋሰስ ሕዝቦችን እንደሚጎዳና አኗኗራቸውንም እንደሚቀይር፣ በኢትዮጵያና በኬንያ ድንበር ለሚገኘው ቱርካና ኃይቅ ዋነኛ ገባር ወንዝ እንደመሆኑ ሐይቁ ላይ ኑሯቸውን ለመሠረቱ ኬንያውያን ጉዳት የሚያደርስ መሆኑን በመጥቀስ ዘመቻ ከፍተው ነበር፡፡
ከዚህ በተጨማሪም በዳውሮ የሚገኘውን የጥቃት መከላከያ ግንብ ቅርስ በመሆኑ ፕሮጀክቱ ይህንን ቅርስ ያጠፋል የሚል ተቃውሞም ቀርቦ ነበር፡፡
ዘመቻው የተቀናጀና ተከታታይ ስለነበር ይህንን ፕሮጀክት ፋይናንስ ለማድረግ ፍላጎት አሳይተው የነበሩት የአፍሪካ ልማት ባንክ፣ የአውሮፓ ኢንቨስትመንት ባንክና ጄፒ ሞርጋን ባንክ ሐሳባቸውን በመቀልበስ ፋይናንስ ማድረጋቸውን ሰርዘዋል፡፡
ኢንጂነር አዜብ የተከፈተው ዘመቻ በተወሰነ ደረጃ በፕሮጀክት መጓተት ላይ ተፅዕኖ ማሳረፉን ተናግረዋል፡፡
የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊ ይህ ፕሮጀክት በየትኛውም መመዘኛ ለሁለቱም አገሮች ሕዝቦች ጥቅም እንጂ ጉዳት የሌለው መሆኑን በመግለጽ፣ በየትኛውም መስዋዕትነት ቢሆን ግንባታው እንደሚካሄድ አስረግጠው ተናግረው ነበር፡፡
የጊቤ ሦስት ከፍተኛው ወጪ የኤሌክትሮ ሜካኒካል ሥራው እንደመሆኑ ዕቃዎቹ በሙሉ በውጭ ምንዛሪ ከውጭ ስለሚገቡ የግድ ብድር ያስፈልግ ነበር፡፡ ሳሊኒ የሚያካሂደው የሲቪል ሥራ በኢትዮጵያ መንግሥት ወጪ የተሸፈነ በመሆኑ፣ ይህ ሥራ ቀጥሎ ብድር ማፈላለጉ ጎን ለጎን ቀጠለ፡፡
ከብዙ ውጣ ውረድ በኋላ የቻይናው ግዙፍ የኤሌክትሪክ ኩባንያ ዶንግ ፋንግ ግሩፕ ወደ ኢትዮጵያ መጣ፡፡ ኩባንያው ፕሮጀክቱን ካጠና በኋላ ከራሱ አገር የገንዘብ ምንጮች ፋይናንስ ይዞ በመምጣት ሥራውን ተረክቧል፡፡
ብድሩን የቻይና መንግሥት ኢንዱስትሪያልና ኮሜርሻል ባንክ (ICBC) በማቅረብ ዶንግ ፋንግ ግሩፕ ሥራውን ተረክቦ ወደ ግንባታ ሲገባ በኢትዮጵያ በኩል ደስታ ሲሆን፣ ፕሮጀክቱ እንዲሰረዝ ሲወተውቱ ለቆዩ መያዶች የሚዋጥ ሐቅ አልነበረም፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ባለፈው ቅዳሜ ታኅሳስ 8 ቀን 2009 ዓ.ም. ይህ ፕሮጀክት በተመረቀበት ወቅት፣ ‹‹ይህ ፕሮጀክት በብዙ ውጣ ውረድ ውስጥ ያለፈ ነው፤›› ሲሉ ፕሮጀክቱ ያለፈበትን አስቸጋሪ መንገድ አስታውሰዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ጨምረው እንደገለጹት፣ ከ20 ዓመት በፊት 180 ሜጋዋት የሚያመነጭ ፕሮጀክት ለመተግበር እንቅስቃሴ ውስጥ ሲገባ ለምናችሁ ነው ይኼ ሁሉ ኃይል መባላቸውን አስታውሰው፣ አሁን ግን አምስት ሺሕ ሜጋዋት ኤሌክትሪክ ለማመንጨት ቢቃረቡም ይህም በቂ እንዳልሆነና የኃይል ማመንጫ ግንባታ በጥልቀት እንደሚቀጥል አስገንዝበዋል፡፡
በአሁኑ ወቅት ኢትዮጵያ ጊቤ ሦስትን ጨምሮ በአጠቃላይ 4,138 ሜጋዋት ኤሌክትሪክ የማመንጨት አቅም ላይ ደርሳለች፡፡ ከተሞች ኢንዱስትሪዎች፣ የግብርና ፕሮጀክቶች በሙሉ በመስፋፋት ላይ ሲሆኑ፣ የኤሌክትሪክ ፍላጎቱም በዚያው ልክ በማደግ ላይ ይገኛል፡፡
ለአብነት ያህል በ2007 ዓ.ም. የአዲስ አበባ ከተማ ብቻውን 150 ሜጋዋት መጠቀም የጀመረ ሲሆን፣ የተለያዩ ግዙፍ ፕሮጀክቶች እያንዳንዳቸው ከመቶ ሜጋዋት በላይ እንዲሰጣቸው እየጠየቁ ይገኛሉ፡፡
የዚያኑ ያህልም ጎረቤት አገሮችም ጂቡቲ፣ ሁለቱ ሱዳኖች፣ ኬንያ፣ ታንዛኒያና የመሳሰሉት የአፍሪካ አገሮች፣ በሌላ በኩል የመንና ሳዑዲ ዓረቢያ ከኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ የሚፈልጉና ያገኙ አገሮች ናቸው፡፡
መንግሥት የወደፊቱን ፍላጎት በማገናዘብ በአሁኑ ወቅት ሁለት ፕሮጀክቶችን በይፋ ለመጀመር እየተዘጋጀ ነው፡፡ እነሱም የባሮ አኮቦ ተፋሰስ የሆነው የገባ ወንዝና የጊቤ ኦሞ ቀጣይ ፕሮጀክት ነው፡፡ ይህ የኮይሻ ፕሮጀክት በዳውሮ ዞንና በኮንታ ልዩ ወረዳ መካከል ይገኛል፡፡ ፕሮጀክቱ 2,160 ሜጋዋት ኤሌክትሪክ ያመነጫል ተብሎ የሚጠበቅ ሲሆን፣ ሳሊኒ ይህን ፕሮጀክት በይፋ ባይረከብም፣ የተለያዩ ዝግጅቶች ከማድረግ አልፎ የአፋር ቆረጣ ውስጥ መግባቱን ከአካባቢው የወጡ መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡
የኢትዮጵያ መንግሥት ይህ ፕሮጀክት ለሳሊኒ የሚሰጠው ፋይናንስ እንዲገኝ ካደገ ብቻ መሆኑን ገልጿል፡፡ በዚህ መሠረት ሳሊን ብድር ማግኘት ቢችልም፣ ብድር አቅራቢው ባንክ ከመንግሥት ጋር የሚያደርገውን ድርድር ባለማጠናቀቁ በይፋ ወደ ሥራ አልተገባም፡፡
የዳውሮ ዞን የአገር ሽማግሌ የሆኑት አቶ በለጠ ከጊቤ ሦስት ባሻገር የኮይሻ ፕሮጀክትም በዞኑ ውስጥ እንደሚካሄድ በመወጠኑ በጨለማ ውስጥ ለቆየው ዳውሮና ለመላው ኢትዮጵያ ኢኮኖሚያዊ ለውጥ ትልቅ ተስፋ አለው ይላሉ፡፡